Articles                                                 መጣጥፍ

  Back Home      Articles          Poems           News              Jokes               Email Us

        THIS WEBSITE IS CURRENTLY BLOCKED IN ETHIOPIA

የቋጠሮ ርዕሠ አንቀጽ
ወያኔ አቶ ልደቱን እንደጠቀመ እርግጠኛ ባንሆንም
አቶ ልደቱ ወያኔን መጥቀማቸው ግን ያፈጠጠ እውነት ነው!!
 

      

ወያኔ አቶ ልደቱን በጥቅም ገዛቸው! ወይም አቶ ልደቱ  ከወያኔ ጠርቀም ያለ የገንዘብ ጥቅም አገኙ የሚለውንና በወሬ ደረጃ የሚንሸራሸሩትን ወቀሳዎች እውነተኝነት ማረጋገጥ ባንችልም። አቶ ልደቱ  የብዙሃኑን የቅንጅት አመራር አካል ውሳኔ አልቀበልም በሚል የወሰዱት አቋምና! በተከታዩም ያደረጉት እንቅስቃሴ! እታገለዋለሁ የሚሉትን ወያኔን እድሜ ያረዘመ! መሆኑን ግን በርግጠኝነት እንናገራለን።

አቶ ልደቱ የፈጸሙት ተግባር ወያኔን እንደ ጠቀመ ! ትግሉንም በመጠኑም ቢሆን እንዳዳከመ ያምናሉ ወይስ አያምኑም የሚል ጥያቄ ቢቀርብላቸው ምን እንደሚመልሱ አይታውቅም፡፤ ይሁን እንጂ መልሳቸው ምንም ይሁን ምንም በቋጠሮ ገጽ እምነት አቶ ልደቱ አይደለም አሁን ገና ከጅምሩም የወሰዱት የብዙሃንን ውሳኔ ያለመቀበል ኢ-ዲሞክራሲያዊና አምባገነናዊ አቋም ወያኔን እንደሚጠቅም አያውቁም  ማለት የዋህነት ይመስለናል።

በአቶ ልደቱ ወቅታዊ አቋም ዙሪያ ስንነጋገር አብይ ጥያቄ ሆነው የሚቀርቡትም እነኚህ ነጥቦች ናቸው።1ኛ አቶ ልደቱ በወሰዱት አቋም ወያኔ እንደሚጠቀምና እድሜውን ሊያራዝም እንደሚችል ከጅምሩም እያወቁ ለምን በአቋማቸው ጸኑ?

2ኛ እውን እንደተጠረጥረው በጥቅም ተገዝተው ሆን ብለው የወሰዱት የማፍረስ አቋም ወይስ እኔ ልብለጥ  አይነት ! የስልጣን እርከኑ አነሰኝ ኩርፊያ ?ለአቶ ልደቱ የጥፋት እንቅስቃሴ ትክክለኛው ምክንያት ወደፊት የሚታወቅ ቢሆንም! አሁን ባለንበት ደረጃ ማለት የምንችለው! አቶ ልደቱ በጥቅም ተግዝተውም ይሁን በባህሪ ችግር በወሰዱት አቋም በተፋፋመው የህዝብ ትግል ላይ መጠኑ ይብዝም ይነስ ውሃ አፍሰዋል!!! የወያኔ እድሜም በኢንችም ብሆን አራዝመዋል!!!

የቋጠሮ ገጽ አቶ ልደቱ አያሌው ላለፉት 14 አመታት ያደረጉትን እንቅስቃሴና በተለይ ወጣቱን ትውልድ ለትግል በማነሳሳት የተጫወቱትን ሚና በእጅጉ ታደንቃለች! ለትግሉ እዚህ ደረጃ መድረስም ታላቅ አስተዋጾ ማድረጋቸውንም ታምናለች! ስለዚህም አቶ ልደቱ ላለፉት በርካታ አመታት ያደረጉት እንቅስቃሴ ሁሉ በወያኔ ጉያ ሥር ተወሽቀው ለጥቅም ሲሉ የህዝብን ትግል የሰለሉበት እንቅስቃሴ ነው የሚለውን አመለካከት የቋጠሮ ገጽ በፍጹም አትጋራም፡፤ እንደሚጠረጠረው አቶ ልደቱ የቅንጅቱን ብዙሃን አመራር ውሳኔ ላለመቀበል ከወሰዱት አቋም ጀርባ ረብጣ ብር የተሸከሙ የወያኔ እጆች ቢገኙ እንኳን መደለያውም ሆነ  የድለላው ስምምነት የቅርብ ግዜ ተውኔት እንጂ የዘመናት እድሜ፡ያካበተ የውስጥ አርበኝነት ገድል አይመስለንም።ይህን ስንል በጥቅም ተደልለው ከሆነ መቼም ተደለሉ መቼ ምንም ለውጥ እንደማያመጣ ጠፍቶን ሳይሆን! ያለፉት የትግል እንቅስቃሴዎቻቸው ከዝህ በወገን ቆመው የታገሉ መሆናቸውን እንደምናምን ለመጠቆም ነው።

 አቶ ልደቱ አያሌው የዲሞክራሲ ዋንኛ መገለጫ የሆነውን ለብዙሃን ውሳኔ መገዛት የሚለውን መመሪያ ለምን ጣሱ? በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ የሠጡት መልስ ከዶሮና እንቁላል ማን ይቀድማል የሚለውን አይነት መልስ የሌለው አዙሪታም አካሄድ በመሄድ ለመመለስ መሞከራቸው! በቋጠሮ ገጽ እምነት አቶ ልደቱ የወሰዱት አቋም ምክንያታዊ ሳይሆን ለግዜው ግልጽ ባልሆነልን ውጫዊ ምክንያት ገፋፊነት እንደተወሰደ የሚያረጋግጥ ነው።

አቶ ልደቱ ለምን ለብዙሃኑ ውሳኔ አልተገዙም ሲባሉ! የሰጡት መልስ እኔም ያልኩት ብዙሃኑ ቀደም ሲል የወሰነው ውሳኔ መሻር የለበትም ነው! የሚል ነበር።
በብዙሃኑ ቀደም ብሎ የወሰነውን ውስኔ መልሶ ሊሽረውም እንደሚችል እያወቁና አናሳው የሳቸው ጎራ ለብዙሃኑ ውሳኔ መሻር ወገቡን ይዞ የመከራከር መብት ሊኖረው እንደማይችልና አስራሩም ከዲሞክራሲዊ ህግጋት ያፈነገጠ   መሆኑን እየተረዱ!!ይህን ማምለጫ ምክንያት መሰንዘራቸው!  አቶ ልደቱ ድብቅ የጥፋት ሚስጥር እንዳልቸው እንደንጠረጥር ያስገደደን ሌላው ነጥብ ነው፡፤

በቋጠሮ ገጽ እምነት አቶ ልደቱ ተደልለውም ይሁን በስልጣን እርከን ማነስ ሳቢያ በተፈጠረ ቅሬታ ተነሳስተው ይሁን! የፈጸሙት ተግባር በህዝብ ትግል ላይ መጠነኛም ቢሆን ጥፋት አድርሷልና !! ከትግሉ ጎራ መገለላቸው ትክክል ነው። ወደ ፊትም ወደ ትግሉ ጎራ ሊቀላቀሉ አይገባም።

በጥቅም ተገዝተው ከሆነ ታሪክ ይፈርዳቸዋል በስልጣን እርከን ቅሬታ ተስምቷቸው የወሰዱት እርምጃ ከሆነም ከሕዝብ ጥቅም በበለጠ ለግል ስልጣን የሚታገሉ ሰው ናቸውና በመጻዊ የኢትዮጵያ ፖለቲካ ህይወት ውስጥ ሊሳተፉ አይገባቸውም እንላለን።

በመጨረሻም የህዝብ ትግል ያደራው በህዝብ መብት ዙሪያ እንጂ በግለሰብ ዙሪያ አይደለምና የአቶ ልደቱ ከትግሉ እንቅስቃሴ መገለል ራሳቸውን ብቻ የሚያገል እንደሆነ የቋጠሮ ገጽ እምነት ነው፡፤ አቶ ልደቱ ባደረጉት እንቅስቃሴ የተቸራቸውን ክብር ሁሉ በጥፋታቻው ተነጥቀዋል፡፤ ህዝባዊ ትግል ያሰራለትን አክብሮ ያሴረበትንም አስወግዶ የነገውን የትግል ሪትም ብቻ ተከትሎ ሁሌም ወደፊት የሚተም እንጂ ከታሪክና ከባለታሪክ ጋር ፍቅር እስከመቃብር ብሎ መቀመቅ የሚወርድ አይደለምና! የአቶ ልደቱንም ታሪክ የውሾን ነገር ያነሳ ብለን ትግሉን ማፋፋም አለብን! እንላለን።